Bete Amhara

Bete Amhara

Thursday, July 2, 2015

ቤተ አማራ የሚለው ጽንሰ ሃሳብ እንዴት መጣ?

ቤተ አማራ የሚለው ጽንሰ ሃሳብ እንዴት መጣ?
**************************************************************************************
ዛሬ የወንድማችን የመለክ ሃራ የልደት በአልን በደመቀ ሁኔታ እያከበርን እንገኛለን። መለክ ሃራ እና ቤተ አማራ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ናቸው። መለክ የቤተ አማራ ነጻ መንግስት የመመስረት አስፈላጊነትን በየካቲት 7, 2007 ዓ.ም ለውይይት ሲያቀርብ ከየአቅጣጫው ከፍተኛ ተቃውሞ ደርሶበት እንደነበር ብዙዎቻችን እናስታውሳለን። ይሁን እንጅ ጊዜያት በነጎዱ ቁጥር በተነሳው ሃሳብ ሰዎች መከራከር እና መወያየት ሲጀምሩ የቤተ አማራ መንግስት ምስረታ ጉዳይ እንደ ጠዋት ጸሃይ ፍንትው ብሎ ሊታይ ችሏል። በዚያን ጊዜ ካለማጋነን አምስት ወይንም ስድስት ልጆች ብቻ በሃሳቡ ዙሪያ የተስማማን ብንሆንም ዛሬ ላይ ግን በዋናው የቤተ-አምራ የፌስቡክ አካውንት ብቻ ከ12,000 በላይ ተከታዮችን ማፍራት ችለናል። ይህ ከተመሰረተ የአምስት ወራት እድሜ ብቻ ያስቆጠረው ጎጇችን የዛሬ አመት የልደት በአላችንን ስናከብር በ10 እጥፍ አድጎ እንደምናየው እና ህዝባዊ ማእበሉም እንደማይቆም ሙሉ እምነት አለን። ግና ለዚህ ሁሉ ህዝባዊ ንቅናቄ ስኬት መነሻ ምክንያት የሆነው ከታች የምታነቧት የወንድማችን የመለክ ሃራ ጽሁፍ ነች።
ጽሁፏን ድጋሜ ለመለጠፍ ስንነሳ በሁለት ምክንያቶች ነው። አንደኛ ስለቤተ አማራ እንቅስቃሴ ምንነት ፤ መነሻ ምክንያቶች እና አላማዎች የሚጠይቅ ህዝብ በየቦታው እየበዛ በመሆኑ እንደማጣቀሻ ለመጠቀም ብሎም በእያንዳንዱ የቤተ አማራ ቤት እንድትደርስ እድሉን ለመክፈት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ታሪካዊነቷን አስጠበቆ ወንድማችን ላደረገው ድንቅ ስራ እውቅና ለመስጠት ነው። ይህንን የምታነቡ ሁሉም የቤተ አማራ ቤተሰቦች በየገጾቻችሁ share በማድረግ ላልደረሰው ታዳርሱ ዘንድ በትህትና እንጠይቃለን።
*ማስታወሻ*
መገንጠል የሚለው ቃል ለዚህች ሰነድ ታሪካዊነት ማስሻ ብቻ የተቀመጠ እንጅ ከእንግዲህ ቃሉ የተቀየረ እንደሆነ እና ጥቅም ላይ እንደማይውል ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ በምትኩ ከእንግዲህ የምንጠቀምበት ፍሬ ቃል “የአማራ ነጻ መንግስት ምሥረታ” እንዲሆን በትህትና እናሳስባለን፡
አማራን ስለመገንጠል የቀረበ የውይይት ሀሳብ
===============================
ብዙ የአማራ ልጆቸ መገንጠል ሲባል እንደነግጣለን፡፡ ድንጋጤአችን ግን አግባብ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ የተባለውን ቅርጽ እንወዳለን፡፡ ተገቢ ነው፡፡ አገርን መውደድ ተገቢ ነው፡፡ በደምና በአጥንት የተገነባች አገር በመሆንዋ እንወዳታለን፡፡ የአባቶቻችን አጥንት ያላረፈበት ቦታ የለም፡፡ ስለዚህም ከኢትዮጵያ ጋር ታሪካዊ፡ ባህላዊ፡ ስነልቡናዊ እና ደማዊ ወይም ተፈጥሮአዊ ትስስር አለን፡፡ ከዛም አልፎ መላዋን ኢትዮጵያ ትልቅና ሰፊ እንዲሁም ሀያል አገር የማድረግ ህልም አለን፡፡ በዚህም ሳቢያ ከኢትዮጵያ ጋር ያለን ትስስር ከትናንት ብቻም ሳይሆን ከነገም ጋር ነው ማለት ነው፡፡ ይህ ሁሉ መልካም ነገር ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ ሁሉ እንዲኖር አማራ የሚባል ህዝብ መጥፋት አለበት ወይስ መኖር አለበት የሚል መስቀለኛ ጥያቄ እፊታችን ላይ ተደቅኗል፡፡
አሁን ያለንበት ሁኔታ የተዘረዘሩትን እንዳቸውንም እንድናሳካ የሚያስችለን አይደለም፡፡ በተግባር የምናመጣው ወይም የምንጨብጠው ነገር የለም፡፡ የተዘረዘሩት መልካም ነገሮች ህልም ብቻ ናቸው፡፡ ስለዚህ ህልማችንን እየበላን እያጠፉን ባሉ ሀይሎች ዘራችን ይጥፋ ወይስ ከህልማችን ነቅተን ተጨባጩን እውነት ብቻ በመረዳት ራሳችንን እናድን? ይህ በእውነቱ የመኖርና ያለመኖር፤ ህልውናችንን የሚወስን፤ መመለስ ያለበት ጥያቄ ነወ፡፡ ሲጨመቅም እንኑር ወይስ እንጥፋ የሚል የውሳኔ ወኔን የሚጠይቅ ነው፡፡ ከቅርቡ ብንጀምር ከአጼ ፋሲል ጀምሮ ትልቅ አገርነትን ስንመኝ ኖርን እንጅ አልተሳካልንም፡፡ ከአንድም ሁለት ሶስት ጊዜ ራሳችንን ለጠላት አሳልፈን ከመስጠት በቀር የፈይድነው ነገር የለም፡፡ በቴዎድሮስ እስከ ኢየሩሳሌም ድረስ ህልም አለምን፡፡ ነገር ግን ምንም ሳንፈይድ በአጭር ቀረን፡፡ ከዛ በኋላ በመጡት መሪዎቻችንም ብዙ ታሰበ፡፡ ግን በአጭር ቀረን እንጅ አንድ ስንዝር ፈቅ አላልንም፡፡ አንድ ወጥ ማህበረሰብ ለመፍጠር ጣርን፡፡ አልተሳካም፡፡ በመላዋ ኢትዮጵያ የሚገኙ ብሄረሰቦችን ለማቻቻልና አስማምቶ ለማኖር ብዙ ደከምን፡፡ ግን ምን አተረፍን? ስንል ጠላትነታቸውን ብቻ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ከዚህ ሁሉ አንዱም ያልተሳካው ለምንድን ነው? ብለን ስንጠይቅ ካለፉት መሪዎቻችን ጀምሮ የማይጨበጥ ህልም የሚያጠቃን በመሆናችን ነው፡፡ ልናደርግ የምንችለውንና የማንችለውን ከእቅማችንና ከነባራዊ አካባቢያችን ጋር አመዛዝነን መራመድ ባለመቻላችን ነው፡፡ ሁልጊዜ የምናስበው ህልማችንን ነው እንጅ በህልማችን መሀል የተጋረጠውን እውነተኛ እንቅፋት አናየውም፡፡ አያቶቻችን ሽህ ጊዜ ተሳሳቱ፡፡ እኛንም የዛው ስህተት ቀጣይ ክፍል አንቆ ይዞናል፡፡ ህልምና እውነት መለየት ሳንችል በመቅረታችን ዘራችን እስከመጥፋት ጫፍ ላይ ደረስን፡፡ የሰራነው ሁሉ በክፉ ተባዝቶ እየተመለሰልን ነው፡፡ አንገታችን አንድ ቢሆንለት ቆርጦ ሊጥለን ከሚከጅለው ግለሰብ አንስቶ በጅምላ ሊፈጀን እስከሚዘጋጀው ድርጅት ድረስ ጥፋት ተደግሶልናል፡፡ በየቤቱ ቢላ እየሳለልን ያለውን ቤቱ ይቁጠረው፡፡ እንግዲህ ከእንቅልፉ የሚነቃ ይንቃ፡፡ አልነቃም ያለ ለራሱ ይተኛ፡፡ እኛንም ሊያስተኛን አይሞክር፡፡
እና ምን እናድርግ?
1) መገንጠል ለምንድን? የምንገነጠለው ተመችቶን ወይም ደልቶን አይደለም፡፡ ህይወታችንን ለማዳንና ዘራችንን ለማስቀጠል ነው፡፡ መገንጠል በአሁኑ ሰአት የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ ግለሰቦችም ሆኑ ድርጅቶች ሊጠፉን እየፈለጉ እየተዘጋጁ ናቸው፡፡ ይህም በተለያዩ ቦታዎች በማንነታችን ብቻ ማለትም አማራ በመሆናችን ብቻ በሚደርሱ ጭፍጨፋዎች፤ ቤት ተዘግቶ እስከነፍስ መቃጠል፤ መዘረፍ፤ መገለል፤ መሰደብ፤ ከስራ መባረር፤ መነቀፍ፤ መጠላት፤ መታሰር፤ መገደል፤ መሰቃየት፤ መገፋትና ከእድገት መታገድ እንዲሁም ከነገ ተስፋ ጋር ፈጽሞ መቆራረጥ በቂ ምልክቶች ናቸው፡፡ ይህ ሁሉ ያልደረሰበት አማራ ካለ ይህ ጽሁፍ አይመለከተውም፡፡ ወይም ሎሌ ነው፤ አልያም አማራ አይደለም፡፡ እነዚህ ምልክቶች ናቸው፡፡ በብዙ ቦታዎች የዘር ማጥፋት ተደርጓል፡፡ በክልሉ ውስጥም የተለያዩ ልንናገራቸው ጊዜው ያልሆነ የዘር ማጥፋት ድርጊቶች ተፈጽመዋል፡፡ ይህ ሁሉ እየሆነ ያለው እንግዲህ ገና ተሰባስበን ለማንም እውነተኛ ስጋት ሳንሆን ነው፡፡ ግፉ እየጨመረ በመጣበት በአሁኑ ወቅት ተሰባስበን እውነተኛ ራሳችንን ማስከበር የሚስችል አቅም መገንባት ብንችል ምን ሊያደርጉን እንደሚችሉ ከዚህ ተነስቶ መገመት ነው፡፡ ነገር ግን በጅምላ ያጠፉናል ብለን ከመደራጀት ወደኋላ አንልም፡፡ በጅምላ ባንጠፋም ቀስ በቀስ በዘዴ መጥፋታችን አይቀርም፡፡ ስለዚህ ሁለቱም አይነት ጥፋት ጥፋት ነው፡፡ በሁለቱም መንገድ ልንጠፋ መሆኑ እርግጥ ከሆነ ዘንዳ መሰባሰቡ የተሸለ አማራጭ ነው፡፡ መሰባሰቡ ሲያጠፉን ይዘን ለመጥፋት ያስችለናል፡፡ አለበለዚያ በተራዘመ ጊዜ በዘዴ ማለቃችን ነው፡፡
2) ለምንድን ነው ይህ ሁሉ የሚደርስብን? ግልጽ ነው፡፡ ተገንጣይ ድርጅቶች ላይ ኢትዮጵያ ኢትዮጵያ እያልን እንቅፋት ስለሆንን ነው፡፡ ወያኔና ኦነግ እኛን ለማጥፋት የዶለቱት በዚህ ስጋታቸው ነው፡፡ በተለይ ወያኔ ተግቶ እያጠፋን ያለው የእርሱን የትግራይ ሪፑብሊክ መመስረት አማራ ነው የሚደናቅፈን ብሎ ስለሚሰጋ ነው፡፡ ከአያያዛቸው እንደምናየው ከአርባ አመት በፊት ጀምሮ ይዘፍኑ የነበረውን ዘፈን አልቀየሩም፡፡ የድርጅታቸውም ስም አልተቀየረም፡፡ ይህም የሪፑብሊክነት አላማቸው ጠረጴዛ ላይ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ይህ ማለት ደግሞ በአማራ መቃብር ላይ የትግራይ ሪፑብሊክ ትገነባለች የሚለው የጥፋት አላማ እስከነነፍሱ አለ ማለት ነው፡፡ የዚሁም ማሳያው እያደረጉት ያለው ግዛትን የመንጠቅና የማስፋት እርምጃ ከበቂ በላይ ማስረጃ ነው፡፡ ጠቅላላ የአየሩ ሽታም አደገኝነት አለው፡፡ ከሌሎች ብሄረሰቦች ጋር የሚያጣሉንና በተለይ በአሁኑ ሰአት እየተባባሰ መምጣቱም ለመጨረሻው ጥፋት እያዘጋጁን ይመስላል፡፡ ስለዚህ እኛ አቋም ቀይረን የራሳችንን ግዛት ብቻና ህዝባችን ይዘን ብንቀመጥ ይህ ሁሉ እየተሳለ ያለው ሰይፍ ወደሰገባው ይመለስ ይሆናል፡፡ በእነርሱ ላይ ያለንን እንቅፋትነት ማቆም አለብን፡፡ እነርሱም ይሂዱ እኛም የራሳችንን ይዘን በጊዜ በደህና እንሰነባበት፡፡ ሳይረፍድ የምናደርገውን አሁን እናድርግ፡፡
3) ብንገነጠል ምን ይደርስብናል? በድንበር አካባቢዎች ግጭት ሊያጋጥመን ይችላል፡፡ ይህ ታሳቢ ስጋት ነው፡፡ ሲደርስ እንዳመጣጡ እንፈታዋለን፡፡ የባህር በር ሊያስፈልግ ይችላል፡፡ አሁንም የለንም፡፡ በኋላም አዲስ ነገር አይሆንም፡፡ ከአፋርና ከኤርትራ ጋር በመስማማት የባህር በር ልናገኝ የምንችልበት እድል ሰፊ ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን ትግራይ የወሰደብን መሬት ሲመለስ ከኤርትራ ጋር በቀጥታ ያገናኘናል፡፡ በዚህ ሰፊ ድንበር ከኤርትራ ጋር በምናደርገው ስምምነት የባህር በር ማግኘት እንችላለን፡፡ ባናገኝም የሚደንቅ አይደለም፡፡ አሁን እየኖርንበት ካለው የከፋ አይሆንምና፡፡
4) ብንገነጠል ምን እንጠቀማለን፡፡ ከጥላቻ እንላቀቃለን፡፡ የራሳችንን ህዝብ በፍቅርና በሰላም እያኖርን በሰላም እንኖራለን፡፡ ከግድየያና እስራት እንገላገላለን፡፡ ዘራችን ከመጥፋት አደጋ እንድናለን፡፡ አጠቃላይ የሰውና የቁሳዊ ሀብታችንን በመጠቀም ማደግ እችላለን፡፡ እዚህ አገር ለሚደርስ ሰው ሰራሽም ሆነ የተፈጥሮ ችግር ተጠያቂ ከመሆን እንድናለን፡፡ ያለስጋትና ጭንቀት ባለን ነገር ላይ እየጨመርንበት እየተሳሰብን እንኖራለን፡፡ ኢትዮጵያ ከምንለው አገር ጋር ተያይዞ የሚደርስብን መከራ ሁሉ ያቆማል፡፡ የማንንም እዳ ስንከፍል አንኖርም፡፡ ብንሞትለትና ብንደክምለት ለሚያመሰገነን ጎስቋላ ወገናችን ብንኖርለት የህሊና እረፍት፤ የመንፈስ እርካታ ነው፡፡ ለጎስቋላና በሁሉ ዘንድ እኒዲጠላ ተደርጎ ሞት የሚደገስለትን ህዝብ ታድጎ እና እያገለገሉ መኖር ከምንም በላይ ዋጋ አለው፡፡ ከምንም ነገር ጋር ሊወዳደር አይችልም፡፡ የመኖራችን ሁሉ ምክንያት ይሄው ሊሆን ይገባዋል፡፡
5) እንደአገር መቆም እችላለንን? በደንብ፡፡ እንደአገር ሊያኖሩን የሚችሉ ሁሉም ነገሮች አሉን፡፡ አገርን የሚያሳድገው ጠንካራ ትምህርት ነው፡፡ ህዝባችን በእውቀት የሚያምን ህዝብ በመሆኑ ይህንኑ በማበረታታት በእውቀት የሚያምንና በእውቀት የሚመራ ማህበረሰብ መፍጠር እችላለን፡፡ ሀይቆችና ወንዞች አሉን፡፡ በእነርሱ እናለማለን፡፡ ሰሜን ወሎንና ደቡብ ጎንደርን በተለይም እምብዛም የማያበቅሉ አካባቢዎችን ከተሞች በማድረግ ለም አካባቢዎችን ለእርሻ ብቻ እናውላለን፡፡ የእርሻ ምርታችን በቴክኖሎጅ በማገዝ ከእኛ ፍጆታ በላይ ማምረት እንችላለን፡፡ አሁንም አርሰን ነው የምንበላው፡፡ በኋላም አርሶ መብላት ነው፡፡ እንዴያውም ያኔስ ማንም ሳይዘርፈን ለራሳችን ብቻ እንጠቀማለን፡፡ እዚህ ጋ የሰሊጥ ምርታችን ከቡና ጋር እኩል የውጭ ገቢ የሚያስገኝ መሆኑን ልጠቁም እወዳለሁ፡፡ ምድራችን ማናቸውንም የምንፈልገውን ነገር ታበቅላለች፡፡ በደህና ቀን የተማረ ህዝብ ስላለን እርሱን ወገኑን የሚረዳበትን መንገድ እናመቻቻለን፡፡ በተለይ ከክልላቸው ውጭ የሚኖሩ አማሮች አብዛኞቹ የተማሩ በመሆናቸው እነርሱ በጣም ያግዙናል፡፡ ሁሉንም ወደ እናት ምድራቸው እንመልሳቸዋልን፡፡ ቀድሞውንም የዳበረውን የህዝባችን ባህል በማበረታታትና በሳይንስ በመደገፍ ጠንካራና የተደላደለ እነናደርገዋለን፡፡ በውጭ የሚኖሩ ከሁለት ሚሊዮን በላይ አማሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ አብዛኞቹም በእውቀታቸውና በገንዘባቸው ሊያግዙ የሚችሉ ትልቅ መተማመኛዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ የምንጠጣው ውሀ፤ የተማረ ህዝብ፤ ሰፊ ቁጥር ያለው ዲያስፖራ፤ ያደገ ማህበራዊ ስነልቡናና ባህል ያለው ህዝብ፤ ለመማር ዝግጁ የሆነ ህዝብ፤ ይዘን አገር መገንባት ቀላል ነው፡፡ አገራችን በተለይ በሁለት ዋና ዋና ምሰሶዎች ፀንቶ መቆም ይችላል፡፡ በሳይንስ የተደገፈ ግብርናና ጠንካራ ትምህርት ላይ፡፡
6) መንገዱን እንዴት እንሂደው? ማንኛውም የአማራ ልጅ በማህበራዊ መገናኛም ይሁን በአካል በሚያደርገው ንግግር ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት፡፡ ከአሁኑ ጀምሮ ማንንም አለምሰደብ፤ አለመተቸት፤ በጠቅላላው መቆጠብ መመሪያችን መሆን አለበት፡፡ ሌሎችን በተጋጨን ቁጥር የጠላታችንን ስራ እየሰራንለት እንደሆነ መገንዘብ አለብን፡፡ የእኛ እርምጃ የስሜታዊ እሰጥ አገባ አይደለም፡፡ በመርህ የተመሰረተ የራሱ ግብ ያለው እርምጃ ነው፡፡ ሰከን ባለ አስተሳሰብ ነገሮችን በማጥናት ማንንም ሳንነካ በትእግስት ወደመጨረሻው ግባችን መድረስ ብቻ ነው አላማችን፡፡ ብልህ መሆን ያስፈልጋል፡፡ ማንንም ሳንነካ ራሳችንን ማንቃት፤ ማደራጀትና መመካከር እንችላለን፡፡ አንዱ አማራ ሁሉም አማራ፤ ሁሉም አማራ አንድ አማራ ነው ከአሁን ጀምሮ፡፡ አንዱ ስለሁሉም ይሞታል፤ ሁሉም ስለአንዱ ይሞታለል፡፡ ይህ የፍቅራችንና የአንድነታችን መለኪያ ነው፡፡
7) አማራ ማን ነው? አማራን ስንገነጥል በሂደቱም ሆነ በውጤቱ መሳተፍ የሚፈልግና ራሱን እንደአማራ የሚቆጥር ማናቸውም ሰው ተቀባይነት ይኖረዋል፡፡ በደም ትንሽም ብትሆን የአማራ ጠብታ ያለችበት አማራ ነው፡፡ ከደም ውጭ በአማራ ባህል የሆነ ሰው በባህል አማራ በመሆኑ ተቀባይነት ይኖረዋል፡፡ በአማራ ምድር ውስጥ የሚኖሩ ማናቸውም ግለሰቦችም ሆኑ ንኡሳን ነገዶች አማራ ናቸው፡፡ አማራነትን ለሚፈልግ ሁሉ በሩ ክፍት ነው፡፡ ስለዚህ በደምም ሆነ በባህል አማራ የሆነ ማናቸውም ሰው አማራ ነው፡፡ ከአማራ ጋር ጥብቅ የባህልና የደም ትስስር ያላቸው የሸዋ ኦሮሞ፤ አፋር፤ ሀድያ፤ ከንባታ፤ ከፋ፤ ጉራጌና አርጎባ የምንመሰርተው ነጻ መንግስት አባላ መሆን ይችላሉ፡፡ ነገር ግን በራሳቸው ምርጫ ይወሰናል፡፡
8) የአገራችን ስም ማን ይሆናል? ብዙ ምርጫዎች አሉን፡፡ ከእነርሱም አማራ፤ ቤተ አማራ፤ አቢሲኒያ፤ ኢትዮጵያ፤ ግዮን ናቸው፡፡ ከእነዚህ ሁሉ ህዝቡ የፈለገውን በአገራችን ስምነት ልንቀበለው እንችላለን፡፡
9) ሰንደቅ አላማችን? ንጹሁን ሰንደቅ አላማችን ልናደርግ እችላለን፡፡
10) ድንበራችን? ታሪክ ተመርምሮ በድርድር የሚወሰን ድንበር ይኖራል፡፡ በሀይላችን መጠን የሚወሰን ይኖራል፡፡
11) የመንግስታችን አይነት? ያለጥርጥር ሴኩላር መንግስት እንመሰረታለን፡፡ ዲሞክራሲያዊ ስርአት እንገነባለን-ሳይሸራረፍ ሳከለስ፡፡
12) የአስተዳደር ክልል? ሸዋ፤ ጎንደር፤ ጎጃምና ወሎ ተብለው በጥንት ስማቸው ይቀጥላሉ፡፡
መለክ ሐራ